የጋብቻ ሁኔታዎች አለመሟላት የሚያስከትለው ውጤት


የጋብቻ ሁኔታዎች አለመሟላት የሚያስከትለው ውጤት

አንቀጽ ፴፩ የዕድሜ ሁኔታ

 

፩. በዚህ ሕግ አንቀጽ ፯ ንዑስ አንቀጽ (፪) የተደነገገው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ዕድሜአቸው ከአሥራ ስምንት ዓመት በታች በሆኑ ሰዎች መካከል የተፈፀመ ጋብቻ በማንኛውም ባለጉዳይ ወይም በዐቃቤ ሕግ ጥያቄ እንዲፈርስ ይደረጋል፡፡

፪. ሕጉ የሚጠይቀው የጋብቻ ዕድሜ ከተሟላ በኋላ ጋብቻው እንዲፈርስ ጥያቄ ማቅረብም ሆነ መወሰን አይቻልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፪ የሥጋ ወይም የጋብቻ ዝምድና

በሥጋ ወይም በጋብቻ ዝምድና ምክንያት ጋብቻ እንዳይፈጸም የተደነገገውን ክልከላ በመተላለፍ የተፈጸመ ጋብቻ በማንኛውም ባለጉዳይ ወይም በዐቃቤ ሕግ ጥያቄ እንዲፈርስ ይደረጋል፡፡

 

አንቀጽ ፴፫ በጋብቻ ላይ ጋብቻ

 

፩. በጋብቻ ላይ ሌላ ጋብቻ ተፈጽሞ የተገኘ እንደሆነ በመጀመሪያው ወይም በሁለተኛው ተጋቢ ወይም በዐቃቤ ሕግ ጥያቄ የኋለኛው ጋብቻ እንዲፈርስ ይደረጋል፡፡

፪. ሆኖም የመጀመሪያው ተጋቢ የሞተ እንደሆነ የኋለኛው ጋብቻ እንዲፈርስ መጠየቅ አይቻልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፬ በፍርድ ክልከላ ምክንያት ጋብቻን ስለማፍረስ

 

፩. በፍርድ የተከለከለ ሰው ፍርድ ቤት ሳይፈቅድ ጋብቻ ፈጽሞ የተገኘ እንደሆነ፣ የተከለከለው ሰው ራሱ ወይም አሳዳሪው ጋብቻው እንዲፈርስ ጥያቄውን ለፍርድ ቤት ማቅረብ ይችላል፡፡

፪. የተከለከለው ሰው ጋብቻው እንዲፈርስ የሚያቀርበው ጥያቄ ክልከላው ከቀረበት ቀን ጀምሮ ስድስት ወር ካለፈ በኋላ ሊቀርብ አይችልም፡፡

፫. ጋብቻው እንዲፈርስ በአሳዳሪው የሚቀርበው ጥያቄ ጋብቻው መፈፀሙን ከአወቀበት ቀን ጀምሮ ከስድስት ወር በኋላ ወይም በማናቸውም ምክንያት ቢሆን ክልከላው ከቀረ በኋላ ሊቀርብ አይችልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፭ በኃይል ተግባር የተፈፀመ ጋብቻን ስለማፍረስ

 

፩. ማንኛውም ሰው ተገዶ ጋብቻ የፈጸመ እንደሆነ ጋብቻው እንዲፈርስ ጥያቄውን ለፍርድ ቤት ማቅረብ ይችላል፡፡

፪. ስለዚህ ጉዳይ የሚቀርበው ጥያቄ የኃይል ሥራው ከቀረበት ከስድስት ወር በኋላ እና በማናቸውም ምክንያት ቢሆን ጋብቻው ከተፈፀመ ከሁለት ዓመት በኋላ ሊቀርብ አይችልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፮ በስህተት ምክንያት የተፈጸመ ጋብቻን ስለማፍረስ

 

፩. ማንኛውም ሰው ከመሠረታዊ ስህተት በመነሳት ጋብቻ የፈፀመ እንደሆነ ጋብቻው እንዲፈርስ ጥያቄውን ለፍርድ ቤት ማቅረብ ይችላል፡፡

፪. ስለዚህ ጉዳይ የሚቀርበው ጥያቄ መሳሳቱን ከአወቀበት ቀን ጀምሮ ከስድስት ወር በኋላ እና በማናቸውም ምክንያት ቢሆን ጋብቻው ከተፈፀመ ከሁለት ዓመት በኋላ ሊቀርብ አይችልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፯ በብቸኝነት ለመኖር የተወሰነውን ጊዜ ስላለመጠበቅ

 

በዚህ ሕግ አንቀጽ ፲፮ ንዑስ አንቀጽ (፩) የተመለከተው በብቸኝነት ለመኖር የተወሰነው ጊዜ አልተከበረም በሚል ምክንያት ብቻ ጋብቻ እንዲፈርስ ጥያቄ ሊቀርብ አይችልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፰ የክብር መዝገብ ሹም ሥልጣን የሌለው ስለመሆኑ

 

ጋብቻው ያስፈጸመው የክብር መዝገብ ሹም በአንቀጽ ፳፪ መሠረት ሥልጣን አልነበረውም በማለት ብቻ ጋብቻው እንዲፈርስ ለመወሰን አይቻልም፡፡

 

አንቀጽ ፴፱ የሥነ ሥርዓት አለመጠበቅ

 

በዚህ ሕግ አንቀጽ ፳፭ ንዑስ አንቀጽ (፫) እና (፮) የተመለከቱት ሥርዓቶች አልተጠበቁም በማለት ብቻ ጋብቻ እንዲፈርስ ሊወሰን አይችልም፡፡

Leave a Reply

Please log in using one of these methods to post your comment:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.